Abstract:
የጥናቱ ዋና አላማ በኢትዮ ሚሊኒየም 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ6ኛ ክፍል ተማሪዎች በ2013 ዓ.ም የመደገፍ ብልሃቶች የአንብቦ መረዳት ችሎታንና የማንበብ ተነሳሽነትን መፈተሽ ነው፡፡ የጥናቱ ዘዴ መጠናዊ ሲሆን የተከተለው የምርምር ስልትም ባለሁለት ቡድን ምሥለ ፍትነታዊ የቅድመና ድኅረ ፈተና ንድፍ ነው። የጥናቱ ተሳታፊዎች በሰሜን ሸዋ ዞን በመርሀቤቴ ወረዳ በዓለም ከተማ ኢትዮ ሚሊኒየም 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በ2013 ዓ.ም ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ከሚገኙት 1,176 ተማሪዎች መካከል ከ6ኛ ክፍል በእድል ሰጪ ንሞና የተመረጡ 80 የ6ኛ “ሀ” እና የ6ኛ “ሐ” ክፍል ተማሪዎች ናቸው። ከሁለቱ ቡድኖች መካከል በመደገፍ ብልሃቶች ስልጠና ታግዘው የሚማሩ ለሙከራ ቡድን የ6ኛ “ሐ” ክፍል 40 ተማሪዎች እና በተለመደው የማስተማሪያ መንገድ (ከብልሃቶች ስልጠና ውጭ) የሚማሩ የቁጥጥር ቡድኑ የ6ኛ “ሀ” ክፍል 40 ተማሪዎች በተራ የእጣ ናሙና አመራረጥ ዘዴ ተመርጠዋል፡፡ ከእነሱም በፈተናና በጽሑፍ መጠይቅ አማካይነት የጥናቱ መረጃዎች ተሰብስበዋል፡፡ የተሰበሰቡት መረጃዎችም በባዕድ ናሙና ቲ-ቴስት (Independent Samples t-test) እና በጥንድ ናሙና ቲ-ቴስት (Paired Samples t-test) ቀመር ተተንትነዋል። መጀመሪያ የሁለቱ ቡድኖች ቅድመ የአንብቦ መረዳት ፈተናና የማንበብ ተነሳሽነት የፅሁፍ መጠይቅ ውጤቶች በባዕድ ናሙና ቲ -ቴስት ተፈትሸው (P>0.05) በሁለቱ ቡድኖች መካከል ጉልህ የአንብቦ መረዳት ችሎታና የማንበብ ተነሳሽነት ልዩነት አለመኖሩ ተረጋግጧል፡፡ በመቀጠልም የሙከራ ቡድኑ ተጠኚዎች በብልሃት ስልጠና የታገዘ፣ የቁጥጥር ቡድኑ ተጠኚዎች ይማሩበት በነበረው ተለምዷዊ ማስተማሪያ ዘዴ (ከብልሃት ስልጠና ውጭ) የአንብቦ መረዳት ትምህርቱን ለአራት ሳምንታት ተምረዋል፡፡ በውጤት ትንተናው መሠረትም የሙከራ እና የቁጥጥር ቡድኖች ድኅረ ትምህርት አንብቦ የመረዳት ፈተናና የማንበብ ተነሳሽነት መጠይቅ አማካይ ውጤት በባዕድ ናሙና ቲ-ቴስት ቀመር እና የሙከራ ቡድኑንም በቅድመ እና በድህረ የአንብቦ መረዳት ፈተናና የማንበብ ተነሳሽነት መጠይቅ አማካይ ውጤት በጥንድ ናሙና ስሌት ሲፈተሽ ውጤቱ (p<0.05) ጉልህ ልዩነት መኖሩ ተረጋግጧል፡፡ ነገር ግን የቁጥጥር ቡድኑ በቅድመ እና በድህረ የአንብቦ መረዳት ፈተናና የማንበብ ተነሳሽነት መጠይቅ በጥንድ ናሙና ስሌት ሲፈተሽ ውጤቱ (P>0.05) ጉልህ ልዩነት አለመኖሩ ተረጋግጧል፡፡ ስለዚህ በመደገፍ ብልሃቶች ስልጠና የታገዘው የአንብቦ መረዳት ትምህርት በተማሪዎች አንብቦ የመረዳት ክሂል እና በማንበብ ተነሣሽነት ላይ የተሻለ ውጤት አስገኝቷል፡፡በጾታዎች መካከልም የጎላ ልዩነት እንደማይታይባቸው በሁለቱም በአንብቦ መረዳትም ሆነ በማንበብ ተነሳሽነት (P>0.05) ከመቁረጫ ነጥቡ በልጦ ተገኝቷል። ስለዚህ የመደገፍ ብልሀቶች በተማሪዎች አንብቦ መረዳት ችሎታና በማንበብ ተነሳሽነት ላይ በወንድና በሴት ተማሪዎች መካከል ልዩነት የለም የሚል አንድምታ ተገኝቷል፡፡እነዚህን ግኝቶች መሰረት በማድረግ መፍትሔ ሰጪ አስተያየቶች ቀርበዋል::